መዝሙር 61 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

የግዞተኛ ጸሎት

ለመዘምራን አለቃ፤ በበገናዎች የሚዘመር፤ የዳዊት መዝሙር

1. እግዚአብሔር ሆይ፤ ጩኸቴን ስማ፤ጸሎቴንም አድምጥ።

2. ልቤ በዛለ ጊዜ፣ከምድር ዳርቻ ወደ አንተ እጣራለሁ፤ከእኔ ይልቅ ከፍ ወዳለው ዐለት ምራኝ።

3. አንተ መጠጊያዬ፣ከጠላትም የምተገንብህ ጽኑ ግንብ ሆነኸኛልና።

4. በድንኳንህ ለዘላለም ልኑር፤በክንፎችህም ጥላ ልከለል። ሴላ

5. አምላክ ሆይ፤ ስእለቴን ሰምተሃልና፤ስምህን የሚፈሩትንም ሰዎች ርስት ለእኔ ሰጠህ።

6. የንጉሡን ዕድሜ አርዝምለት፤ዘመኑንም እስከ ብዙ ትውልድ ጨምርለት፤

7. በእግዚአብሔር ፊት ለዘላለም ይንገሥ፤ይጠብቁት ዘንድ ምሕረትህንና ታማኝነትህን አዘጋጅለት።

8. ስለዚህ ለስምህ ዘወትር ውዳሴ አቀርባለሁ፤ስእለቴንም በየጊዜው እፈጽማለሁ።