7. የሕዝቦች ሁሉ ንጉሥ ሆይ፤አንተን የማይፈራ ማነው?ክብር ይገባሃልና።ከምድር ጠቢባን ሁሉ፣ከመንግሥቶቻቸውም ሁሉ መካከል፣እንዳንተ ያለ የለም።
8. ከከንቱ የዕንጨት ጣዖት ትምህርት የሚቀስሙ ሁሉ፣ጅሎችና ሞኞች ናቸው።
9. የተጠፈጠፈ ብር ከተርሴስ፣ወርቅም ከአፌዝ ይመጣል።ባለሙያውና አንጥረኛው የሠሯቸው፣ብልኀተኞችም ያበጇቸው ሁሉ፣ሰማያዊና ሐምራዊ ልብስ ተጐናጽፈዋል።
10. እግዚአብሔር ግን እውነተኛ አምላክ ነው፤እርሱ ሕያው አምላክ፣ ዘላለማዊም ንጉሥ ነው፤በሚቈጣበት ጊዜ ምድር ትንቀጠቀጣለች፤መንግሥታትም ቍጣውን ሊቋቋሙ አይችሉም።
11. “እናንተም፣ ‘እነዚህ ሰማያትንና ምድርን ያልፈጠሩ አማልክት ከምድር ላይ፣ ከሰማያትም በታች ይጠፋሉ’ ትሏቸዋላችሁ።”
12. እግዚአብሔር ግን ምድርን በኀይሉ ፈጠረ፤ዓለምን በጥበቡ መሠረተ፤ሰማያትንም በማስተዋሉ ዘረጋ።
13. ድምፁን ሲያንጐደጒድ፣ በሰማያት ያሉ ውሆች ይናወጣሉ፤ጉሙን ከምድር ዳር ወደ ላይ እንዲወጣ ያደርገዋል፤መብረቅን ከዝናብ ጋር ይልካል፤ነፋስንም ከግምጃ ቤቱ ያወጣል።
14. እያንዳንዳቸው ጅሎችና ዕውቀት የለሾች ናቸው።ወርቅ አንጥረኛውም ሁሉ በሠራው ጣዖት ዐፍሮአል፤የቀረጻቸው ምስሎቹ የሐሰት ናቸው፤እስትንፋስም የላቸውም።
15. እነርሱ ከንቱ የፌዝ ዕቃዎች ናቸው፤ፍርድ ሲመጣባቸው ይጠፋሉ።
16. የያዕቆብ ዕድል ፈንታ የሆነው ግን እንደነዚህ አይደለም፤እርሱ የሁሉ ነገር ፈጣሪ ነውና፤እስራኤልም የርስቱ ነገድ ነው።ስሙ የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር ነው።
17. አንቺ የተከበብሽ፤ከያለበት ንብረትሽን ሰብስቢ፤
18. እግዚአብሔር እንዲህ ይላልና፤“በዚህች ምድር የሚኖሩትን፣አሁን ወደ ውጪ እወነጭፋቸዋለሁ፤ጒዳቱ እንዲሰማቸው፣መከራ አመጣባቸዋለሁ፤”