መዝሙር 89:12-26 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

12. ሰሜንንና ደቡብን የፈጠርህ አንተ ነህ፤ታቦርና አርሞንዔም በስምህ ሐሤት ያደርጋሉ።

13. አንተ ክንደ ብርቱ ነህ፤እጅህ ኀያል ናት፤ ቀኝ እጅህም ከፍ ከፍ ያለች ናት።

14. ጽድቅና ፍትሕ የዙፋንህ መሠረቶች ናቸው፤ምሕረትና ታማኝነት በፊትህ ይሄዳሉ።

15. እግዚአብሔር ሆይ፤ እልልታን የሚያውቅ፣በፊትህም ብርሃን የሚሄድ ሕዝብ ምስጉን ነው።

16. ቀኑን ሙሉ በስምህ ደስ ይላቸዋል፤በጽድቅህም ሐሤት ያደርጋሉ፤

17. አንተ የብርታታቸው ክብር ነህና፤በሞገስህም ቀንዳችንን ከፍ ከፍ አደረግህ።

18. ጋሻችን የእግዚአብሔር ነውና፤ንጉሣችንም የራሱ የእስራኤል ቅዱስ ነው።

19. በዚያን ጊዜ በራእይ ተናገርህ፤ታማኝ ሕዝብህንም እንዲህ አልህ፤“ኀያሉን ሰው ሥልጣን አጐናጸፍሁት፤ከሕዝብ መካከል የተመረጠውንም ከፍ ከፍ አደረግሁት።

20. ባሪያዬን ዳዊትን አገኘሁት፤በተቀደሰው ዘይቴም ቀባሁት።

21. እጄ ይደግፈዋል፤ክንዴም ያበረታዋል።

22. በጠላት አይበለጥም፤ክፉ ሰውም አይበግረውም።

23. ባላንጣዎቹን በፊቱ አደቅቃቸዋለሁ፤ጠላቶቹንም እቀጠቅጣለሁ።

24. ታማኝነቴና ምሕረቴ ከእርሱጋር ይሆናል፤በስሜም ቀንዱ ከፍ ከፍ ይላል።

25. እጁን በባሕር ላይ፣ቀኝ እጁንም በወንዞች ላይ አኖራለሁ።

26. እርሱም፣ ‘አንተ አባቴ ነህ፤አምላኬና መዳኛ ዐለቴም ነህ’ ብሎ ይጠራኛል።

መዝሙር 89