ዮሐንስ 19:14-24 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

14. ቀኑ የፋሲካ በዓል መዘጋጃ፣ ጊዜውም ከቀኑ ስድስት ሰዓት ያህል ነበር።ጲላጦስም አይሁድን፣ “እነሆ፤ ንጉሣችሁ” አላቸው።

15. እነርሱ ግን፣ “አስወግደው! አስወግደው! ስቀለው!” እያሉ ጮኹ።ጲላጦስም፣ “ንጉሣችሁን ልስቀለውን?” አለ።የካህናት አለቆችም፣ “ከቄሣር በቀር ሌላ ንጉሥ የለንም” ብለው መለሱለት።

16. በመጨረሻም ጲላጦስ እንዲሰቅሉት አሳልፎ ሰጣቸው።ወታደሮቹም ኢየሱስን ይዘው ወሰዱት፤

17. እርሱም የራሱን መስቀል ተሸክሞ በአራማይክ ‘ጎልጎታ’ ተብሎ ወደሚጠራው ‘የራስ ቅል’ ወደተባለው ቦታ ወጣ።

18. በዚያም ሰቀሉት፤ ከእርሱም ጋር ሁለት ሰዎች፣ አንዱን በዚህ በኩል፣ ሌላውን በዚያ በኩል፣ ኢየሱስንም በመካከል አድርገው ሰቀሉ።

19. ጲላጦስም ጽሑፍ ጽፎ በመስቀሉ ላይ አንጠለጠለው፤ ጽሑፉም፣ ‘የናዝሬቱ ኢየሱስ፣ የአይሁድ ንጉሥ’ የሚል ነበር።

20. ኢየሱስ የተሰቀለበት ቦታ ከከተማው አጠገብ ስለ ነበር ብዙዎቹ አይሁድ ጽሑፉን አነበቡት፤ ጽሑፉም፣ በአራማይክና በላቲን፣ በግሪክም ነበር።

21. የአይሁድ የካህናት አለቆች ጲላጦስን በመቃወም፣ “እርሱ፣ ‘የአይሁድ ንጉሥ ነኝ’ እንዳለ ጻፍ እንጂ ‘የአይሁድ ንጉሥ’ ብለህ አትጻፍ” አሉት።

22. ጲላጦስም፣ “በቃ፤ የጻፍሁትን ጽፌአለሁ” ብሎ መለሰ።

23. ወታደሮቹ ኢየሱስን ከሰቀሉ በኋላ፣ እጀ ጠባቡ ሲቀር፣ ልብሱን ወስደው ለእያንዳንዱ አንድ አንድ እንዲዳረስ ለአራት ተከፋፈሉት፤ እጀ ጠባቡም ከላይ እስከ ታች አንድ ወጥ ሆኖ ያለ ስፌት የተሠራ ነበር።

24. ስለዚህ፣ “ዕጣ ተጣጥለን ለሚደርሰው ይድረስ እንጂ አንቅደደው” ተባባሉ። ይህም የሆነው፣“ልብሴን ተከፋፈሉት፤በእጀ ጠባቤም ላይ ዕጣ ተጣጣሉ” የሚለው የመጽሐፍ ቃል እንዲፈጸም ነው።ወታደሮቹ ያደረጉትም ይህንኑ ነው።

ዮሐንስ 19