ዘፀአት 22:9-24 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

9. አንድ ሰው በሬን፣ አህያን፣ በግን፣ ልብስን፣ ወይም ማናቸውንም ንብረት ያለ አግባብ በባለቤትነት ይዞ ሳለ፣ ‘የኔ ነው’ ባይ ቢመጣና ክርክር ቢነሣ፣ ባለ ጉዳዮቹ ነገሩን ለዳኞች ያቅርቡት፤ ዳኞቹ ጥፋተኛ ነው ያሉትም ለጎረቤቱ እጥፉን ይክፈል።

10. “አንድ ሰው አህያ፣ በሬ፣ በግ፣ ወይም ማናቸውንም እንስሳ በጎረቤቱ ዘንድ በአደራ አስቀምጦ ሳለ እንስሳው ቢሞት፣ ወይም ጉዳት ቢደርስበት፣ ወይም ሰው ሳያይ ተነድቶ ቢወሰድ፣

11. በሁለቱ መካከል ያለው አለመግባባት መፍትሄ የሚያገኘው፣ ጎረቤቱ የሌላውን ሰው ንብረት እንዳልወሰደ በእግዚአብሔር (ያህዌ) ፊት በመማል ነው። ባለቤቱም ይህን መቀበል አለበት፤ የካሣም ክፍያ አይጠየቅም።

12. እንስሳው ከጎረቤት ተሰርቆ ከሆነ ግን፣ ለባለቤቱ ካሣ መክፈል አለበት።

13. በዱር አራዊት ተበልቶ ከሆነ፣ ከአውሬ የተረፈውን ማስረጃ አድርጎ በማቅረብ፣ ስለ ተበላው እንስሳ ካሣ እንዲከፍል አይጠየቅም።

14. “አንድ ሰው ከጎረቤቱ እንስሳ ተውሶ ሳለ ባለቤቱ በሌለበት ቢጎዳ ወይም ቢሞት ካሣ መክፈል አለበት።

15. ባለቤቱ ከእንስሳው ጋር ከሆነ ግን፣ ተበዳሪው መክፈል የለበትም፤ እንስሳው ከተከራየም ለኪራይ የተከፈለው ገንዘብ ኪሳራውን ይሸፍናል።

16. “አንድ ሰው ያልታጨችን ልጃገረድ አታልሎ ክብረ ንጽሕናዋን ቢያጎድል፣ የማጫዋን ዋጋ ከፍሎ ሚስት ያድርጋት።

17. እርሷን ለእርሱ የልጅቷ አባት በሚስትነት ለመስጠት ከቶ የማይፈቅድ ቢሆን፣ ለድንግሎች መከፈል የሚገባውን ማጫ አሁንም ቢሆን መክፈል ይገባዋል።

18. “መተተኛ ሴት በሕይወት እንድትኖር አትፍቀድ።

19. “ከእንስሳ ጋር ሩካቤ ሥጋ የሚፈጽም ሰው ይገደል።

20. “ለእግዚአብሔር (ያህዌ) በቀር ለሌላ አማልክት የሚሠዋ ይጥፋ።

21. መጻተኛውን አትበድሉት ወይም አታስጨንቁት፤ እናንተ በግብፅ መጻተኛ ነበራችሁና።

22. “ባል በሞተባት ወይም አባትና እናት በሌለው ልጅ ላይ ግፍ አትዋሉ።

23. ግፍ ብትውሉባቸውና ወደ እኔ ቢጮኹ፣ ጩኸታቸውን በእርግጥ እሰማለሁ።

24. ቍጣዬ ይነሣል፤ በሰይፍም እገድላችኋለሁ፤ ሚስቶቻችሁ መበለቶች፣ ልጆቻችሁም አባት የለሽ ይሆናሉ።

ዘፀአት 22