12. እግዚአብሔር (ያህዌ) ሙሴን፣ “የአንበጣ መንጋ ምድሪቱን እንዲወር ከበረዶ የተረፈውን ሁሉና በማሳም ላይ የበቀለውን ሁሉ ጠርጎ እንዲበላ እጅህን በግብፅ አገር ላይ ዘርጋ” አለው።
13. ስለዚህ ሙሴ በግብፅ አገር ላይ በትሩን ዘረጋ፤ እግዚአብሔርም (ያህዌ) በዚያን ቀንና ሌሊት በሙሉ በምድሪቱ ላይ የምሥራቅ ነፋስ እንዲነፍስ አደረገ፤ በማግሥቱም ነፋሱ አንበጣዎችን አመጣ።
14. እነርሱም ግብፅን በሙሉ ወረሩ፤ ስፍር ቍጥር የሌላቸው ሆነው የሀገሪቱን ዳር ድንበር ሁሉ አለበሱ። እንዲህ ያለ የአንበጣ መዓት ከዚህ ቀደም አልነበረም፤ ወደ ፊትም ደግሞ አይኖርም።
15. ምድሩ ሁሉ ጠቍሮ እስኪጨልም ድረስ አለበሱት። ከበረዶ የተረፈውን በመስክ ላይ የበቀለውንና በዛፍ ላይ ያለውን ፍሬ ሁሉ፣ ጠርገው በሉ። በግብፅ ምድር ሁሉ በዛፍ ላይ ወይም በተክል ላይ አንዳች ቅጠል አልተረፈም ነበር።
16. ከዚያም ፈርዖን ሙሴንና አሮንን በፍጥነት አስጠርቶ እንዲህ አላቸው፤ “በአምላካችሁ በእግዚአብሔር (ያህዌ) በእናንተም ላይ ኀጢአት ሠርቻለሁ፤
17. እንግዲህ አሁን አንድ ጊዜ ደግሞ ኀጢአቴን ይቅር በሉኝና ይህንን ቀሣፊ መዓት እንዲያስወግድልኝ አምላካችሁን እግዚአብሔርን (ያህዌ) ለምኑልኝ።”
18. ሙሴም ከፈርዖን ዘንድ ወደ እግዚአብሔር (ያህዌ) ጸለየ።
19. ከዚያም እግዚአብሔር (ያህዌ) ነፋሱን ወደ ብርቱ የምዕራብ ነፋስ ለወጠው ያም ነፋስ አንበጣዎቹን እየነዳ ወደ ቀይ ባሕር ከተታቸው፤ በግብፅ ምድር በየትኛውም ቦታ አንድም አንበጣ አልቀረም።
20. እግዚአብሔር (ያህዌ) ግን የፈርዖንን ልብ አደነደነ፤ ፈርዖንም እስራኤላውያን እንዲሄዱ አልፈቀደም።
21. ከዚያም እግዚአብሔር (ያህዌ) ሙሴን፣ “በግብፅ ላይ ድቅድቅ ጨለማ እንዲወርድ እጅህን ወደ ሰማይ ዘርጋ” አለው።
22. ሙሴም እጁን ወደ ሰማይ ዘረጋ፤ በመላው ግብፅ ላይ ለሦስት ቀናት ድቅድቅ ያለ ጨለማ ሆነ።
23. በነዚያ ሦስት ቀናት ውስጥ አንዱ ሌላውን ማየት ወይም ከነበረበት ቦታ መንቀሳቀስ አይችልም ነበር። ይሁን እንጂ እስራኤላውያን በሚኖሩበት ስፍራ ሁሉ ብርሃን ነበር።