10. አሮንንና ልጆቹን ሹማቸው፤ እነርሱም ክህነታቸውን ይጠብቁ፤ ሌላ ሰው ማደሪያውን ቢቀርብ ግን ይገደል።”
11. እግዚአብሔርም (ያህዌ) ሙሴን እንዲህ አለው፤
12. “እነሆ፤ በኵር ሆኖ በሚወለደው ሁሉ ምትክ ሌዋውያኑን ከእስራኤላውያን ወስጃለሁ፤ ስለዚህ ሌዋውያን የእኔ ናቸው፤
13. በኵር የሆነ ሁሉ የእኔ ነውና። በግብፅ ምድር በኵር የሆነውን ሁሉ በመታሁ ዕለት ከሰውም ሆነ ከእንስሳ ማናቸውንም የእስራኤልን በኵር ለራሴ ለይቻለሁ፤ የእኔ ይሁን። እኔ እግዚአብሔር (ያህዌ) ነኝ።”
14. እግዚአብሔር (ያህዌ) ሙሴን በሲና ምድረ በዳ፣
15. “ሌዋውያንን በየቤታቸውና በየጐሣቸው ቍጠር፤ የምትቈጥረውም አንድ ወርና ከዚያ በላይ የሆነውን ወንድ ሁሉ ነው” አለው።
16. ስለዚህ ሙሴ በእግዚአብሔር (ያህዌ) ቃል በታዘዘው መሠረት እነዚህን ቈጠራቸው።