24. ሕዝቡ እንደ እንስት አንበሳ ይነሣል፤ያደነውን እስኪያነክት፣የገደለውንም ደም እስኪጠጣ፣እንደማያርፍ አንበሳ ሆኖ ይነሣል።”
25. በዚህ ጊዜ ባላቅ በለዓምን፣ “እንግዲያውስ ፈጽሞ አትርገማቸው፤ ፈጽሞም አትመርቃቸው!” አለው።
26. በለዓምም፣ “እግዚአብሔር (ያህዌ) የሚለኝን ሁሉ ማድረግ እንዳለብኝ አልነገርሁህምን?” ሲል መለሰለት።
27. ከዚህ በኋላ ባላቅ በለዓምን፣ “በል እንግዲያው ወደ ሌላ ቦታ ልውሰድህ፤ ከዚያ ሆነህ እንድትረግምልኝ ምናልባት እግዚአብሔር (ኤሎሂም) ይፈቅድልህ ይሆናል” አለው።
28. ባላቅም በለዓምን ምድረ በዳው ቍልቍል ወደሚታይበት ወደ ፌጎር ጫፍ አወጣው።
29. በለዓምም፣ “ሰባት መሠዊያዎች እዚህ ሥራልኝ፤ ሰባት ኮርማዎችና ሰባት አውራ በጎችም አዘጋጅልኝ አለው።
30. ባላቅም በለዓም እንደ ነገረው አደረገ፤ በእያንዳንዱም መሠዊያ ላይ አንድ ኮርማና አንድ አውራ በግ ሠዋ።