ኤርምያስ 50:9-24 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

9. የታላላቅ መንግሥታትን ማኅበር፣ከሰሜን በባቢሎን ላይ አስነሣለሁ፤እነርሱም በእርሷ ላይ ይሰለፋሉ፤መጥተውም ይይዟታል።ቀስቶቻቸው ባዶ እጃቸውን እንደ ማይመለሱ፣እንደ ሥልጡን ተዋጊዎች ናቸው።

10. የባቢሎን ምድር ትዘረፋለች፤የሚዘርፏትም ሁሉ እስኪበቃቸው ይመዘብሩአታል፤”ይላል እግዚአብሔር።

11. “እናንተ ርስቴን የበዘበዛችሁ ሆይ፤ደስ ስላላችሁና ሐሤትም ስላደረጋችሁ፣በመስክ እንዳለች ጊደር ስለ ፈነጫችሁ፤እንደ ድንጒላ ፈረስ ስለ አሽካካችሁ፤

12. እናታችሁ እጅግ ታፍራለች፤የወለደቻችሁም ትዋረዳለች።እርሷም ምድረ በዳ፣ ደረቅ ምድርና በረሓ፣ከመንግሥታትም ሁሉ ያነሰች ትሆናለች።

13. ከእግዚአብሔር ቍጣ የተነሣ ባድማ ትሆናለች እንጂ፣የሚኖርባት አይገኝም፤በቍስሎችዋም ሁሉ ምክንያት፣በባቢሎን የሚያልፍ ሁሉ ይገረማል፤ ያፌዝባታልም።

14. “እናንተ ቀስት የምትገትሩ ሁሉ፣በባቢሎን ዙሪያ ተሰለፉ፤አንዳች ሳታስቀሩ ፍላጾችን ስደዱባት፤ በእግዚአብሔር ላይ ኀጢአት ሠርታለችና።

15. ከየአቅጣጫው ጩኹባት፤እጇን ትሰጣለች፤ ምሽጓም ይወድቃል፤ቅጥሮቿ ይፈርሳሉ።ይህ የእግዚአብሔር በቀል ነውና፣እርሷን ተበቀሏት፤በሌሎቹ ላይ እንዳደረገችውም አድርጉባት።

16. ከባቢሎን ዘር የሚዘራውን፣በመከር ጊዜ ማጭድ የጨበጠውንም ዐጫጅ አጥፉት፤ከአጥፊው ሰይፍ የተነሣ፣እያንዳንዱ ወደ ገዛ ሕዝቡ ይመለስ፤ወደ ገዛ ምድሩም ይሽሽ።

17. “እስራኤል አንበሶች ያሳደዱት፣የተበተነ መንጋ ነው፤መጀመሪያ የአሦር ንጉሥ፣ቦጫጭቆ በላው፤በኋላም የባቢሎን ንጉሥ ናቡከደነፆር፣አጥንቱን ቈረጣጠመው።”

18. ስለዚህ የእስራኤል አምላክ የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤“የአሦርን ንጉሥ እንደ ቀጣሁት ሁሉ፣የባቢሎንን ንጉሥና ምድሩን እቀጣለሁ።

19. እስራኤልንም ወደ መሰማሪያው እመልሰዋለሁ፤በቀርሜሎስና በባሳን ላይ ይሰማራል፤በኤፍሬም ተራሮችና በገለዓድም ላይ፣እስኪጠግብ ይመገባል።

20. በእነዚያ ጊዜያት፣ በዚያ ዘመን፣”ይላል እግዚአብሔር፤“የእስራኤል በደል ይፈለጋል፤አንዳችም አይገኝም፤የይሁዳም ኀጢአት ይፈለጋል፤ከቶም የለም፤እንዲተርፉ ያደረግኋቸውን ትሩፋን እምራለሁና።

21. “የምራታይምን ምድር፣የፋቁድ ነዋሪዎችንም፣አሳዷቸው፤ ግደሏቸው፤ ፈጽማችሁም አጥፏቸው፤”ይላል እግዚአብሔር፤“ያዘዝኋችሁንም ሁሉ አድርጉ።

22. በምድሪቱ የጦርነት ውካታ፣የታላቅ ጥፋት ድምፅ ተሰማ።

23. የምድር ሁሉ መዶሻ፣እንዴት ተሰበረ! እንዴትስ ደቀቀ!በሕዝቦች መካከል፣ባቢሎን እንዴት ባድማ ሆነች!

24. ባቢሎን ሆይ፤ ወጥመድ ዘርግቼልሻለሁ፤አንቺም ሳታውቂ ተይዘሻል፤ እግዚአብሔርን ተገዳድረሻልና፣ተገኘሽ፤ ተያዝሽም።

ኤርምያስ 50