5. ነገር ግን ራሳችሁን በእኔ ላይ ከፍ ብታደርጉ፣መዋረዴንም እኔን ለመሞገት ብትጠቀሙበት፣
6. እግዚአብሔር እንደ በደለኝ፣በመረቡም እንደ ከበበኝ ዕወቁ።
7. “ ‘ተበደልሁ’ ብዬ ብጮኽ ማንም አይመልስልኝም፤ድምፄን ከፍ አድርጌ ባሰማም፣ ፍትሕ አላገኝም።
8. እንዳላልፍ መንገዴን ዘግቶአል፤መሄጃዬንም በጨለማ ጋርዶአል።
9. ክብሬን ገፍፎኛል፤ዘውዴንም ከራሴ ላይ ወስዶአል።
10. እስክወገድ ድረስ በሁሉ አቅጣጫ አፈራርሶኛል፤ተስፋዬንም እንደ ዛፍ ነቅሎታል።
11. ቍጣው በላዬ ነዶአል፤እንደ ጠላቱም ቈጥሮኛል።
12. ሰራዊቱ ገፍተው መጡ፤በዙሪያዬ ምሽግ ሠሩ፤ ድንኳኔንም ከበው ሰፈሩ።
13. “ወንድሞቼን ከእኔ አርቆአል፤ከሚያውቁኝም ተገለልሁ።
14. ዘመዶቼ ትተውኛል፤ወዳጆቼም ረስተውኛል።
15. የቤቴ እንግዶችና ሴት አገልጋዮቼ እንደ መጻተኛ ቈጠሩኝ፤እንደ ባዕድም ተመለከቱኝ፤
16. አገልጋዬን ብጣራ፣በአንደበቴም ብለምነው፣ አይመልስልኝም።
17. እስትንፋሴ ለሚስቴ እንኳ የሚያስጠላት ሆነ፤የገዛ ወንድሞቼም ተጸየፉኝ።
18. ሕፃናት እንኳ ይንቁኛል፤ባዩኝም ቍጥር ያላግጡብኛል።
19. የቅርብ ወዳጆቼ ሁሉ ተጸየፉኝ፤የምወዳቸውም በላዬ ተነሡ፤
20. ቈዳና ዐጥንት ብቻ ሆኜ ቀረሁ፤ድድ ብቻ ቀርቶልኝ አመለጥሁ።
21. “ወዳጆቼ ሆይ፤ ራሩልኝ፤የእግዚአብሔር እጅ መታኛለችና ዕዘኑልኝ።
22. እግዚአብሔር እንዳሳደደኝ ለምን ታሳድዱኛላችሁ?አሁንም ሥጋዬ አልበቃችሁምን?
23. “ምነው ቃሌ በተጻፈ ኖሮ!በመጽሐፍም በታተመ!
24. ምነው በብረትና በእርሳስ በተጻፈ ኖሮ!በዐለትም ላይ በተቀረጸ!
25. የሚቤዠኝ ሕያው እንደሆነ፣በመጨረሻም በምድር ላይ እንደሚቆም ዐውቃለሁ።