ኢያሱ 10:30-38 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

30. እንዲሁም እግዚአብሔር ከተማዪቱንና ንጉሥዋን በእስራኤል እጅ አሳልፎ ሰጣቸው፤ ኢያሱ ከተማዪቱንና በውስጧ ያለውን ሁሉ በሰይፍ ስለት አጠፋ፤ አንድም ሰው አላስተረፈም፤ በኢያሪኮ ንጉሥ ላይ ያደረገውንም በልብና ንጉሥ ላይ ደገመው።

31. ከዚያም ኢያሱና ከእርሱ ጋር የነበሩት እስራኤላውያን በሙሉ ከልብና ወደ ለኪሶ አለፉ፤ ወጓትም።

32. እግዚአብሔር ለኪሶን አሳልፎ ለእስራኤል ሰጠ፤ ኢያሱም በሁለተኛው ቀን ያዛት፤ በልብና እንዳደረገው ሁሉ እዚህም ከተማዪቱንና በውስጧ ያሉትን ሁሉ በሰይፍ ስለት ፈጃቸው።

33. በዚህ ጊዜ የጌዝር ንጉሥ ሆራም ለኪሶን ለመርዳት መጣ፤ ኢያሱ ግን አንድ እንኳ ሳያስተርፍ ንጉሡንና ሕዝቡን መታቸው።

34. ከዚያም ኢያሱና ከእርሱ ጋር የነበሩት እስራኤላውያን በሙሉ ከለኪሶ ወደ ዔግሎን አለፉ፤ ወጓትም።

35. በዚያኑ ዕለት ያዟት፤ በሰይፍም ስለት አጠፏት፤ በለኪሶ እንዳደረጉት ሁሉ እዚህም በውስጧ የሚገኙትን ፈጽመው ደመሰሷቸው።

36. ከዚያም ኢያሱና ከእርሱ ጋር የነበሩት እስራኤላውያን በሙሉ ከዔግሎን ወደ ኬብሮን ወጡ፤ ወጓትም።

37. ከተማዪቱንም ከንጉሥዋ፣ ከመንደሮቿና በውስጧ ካሉት ጋር ሁሉ አንድም ሰው ሳያስቀሩ በሰይፍ ስለት ፈጇቸው፤ በዔግሎን እንዳደረጉት ሁሉ እዚህም ከተማዪቱንና በውስጧ ያለውን ሁሉ ፈጽመው ደመሰሱ።

38. ከዚያም ኢያሱና ከእርሱ ጋር የነበሩት እስራኤላውያን በሙሉ ወደ ኋላ ተመልሰው ዳቤርን ወጓት።

ኢያሱ 10