ኢሳይያስ 43:6-21 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

6. ሰሜንን፣ ‘አምጣ’፣ደቡብንም፣ ‘ልቀቅ’ እላለሁ፤ወንዶች ልጆቼን ከሩቅ፣ሴቶች ልጆቼንም ከምድር ዳርቻ፣

7. በስሜ የተጠራውን ሁሉ፣ለክብሬ የፈጠርሁትን፣ያበጀሁትንና የሠራሁትን አምጡ።”

8. ዐይን እያላቸው የታወሩትን፣ጆሮ እያላቸው የደነቈሩትን አውጣ።

9. ሕዝብ ሁሉ በአንድነት ይሰብሰብ፤ሰውም ይከማች፤ከእነርሱ አስቀድሞ ይህን የነገረን፣የቀድሞውን ነገር ያወጀልን ማን ነው?ሌሎችን ሰምተው፣ “እውነት ነው” እንዲሉ፣ትክክለኝነታቸውም እንዲረጋገጥ ምስክሮቻቸውን ያቅርቡ።

10. “ታውቁና ታምኑብኝ ዘንድ፣እርሱ እኔ እንደሆንሁ ትረዱ ዘንድ፣እናንተ ምስክሮቼ፣የመረጥሁትም ባሪያዬ ናችሁ” ይላል እግዚአብሔር።“ከእኔ በፊት አምላክ አልተሠራም፤ከእኔም በኋላ አይኖርም።

11. እኔ፣ እኔ እግዚአብሔር ነኝ፤ከእኔም ሌላ የሚያድን የለም።

12. ገልጫለሁ፤ አድኛለሁ፤ ተናግሬአለሁ፤በመካከላችሁ እኔ እንጂ ባዕድ አምላክ አልነበረም።እኔ አምላክ እንደሆንሁ፣ እናንተ ምስክሮቼ ናችሁ” ይላል እግዚአብሔር፤

13. “ከጥንት ጀምሮ እኔው ነኝ፤ከእጄም ማውጣት የሚችል የለም፤እኔ የምሠራውን ማን ማገድ ይችላል?”

14. የእስራኤል ቅዱስ፣የሚቤዣችሁ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤“ስለ እናንተ በባቢሎን ላይ ሰራዊት እሰዳለሁ፤በሚመኩባቸውም መርከቦች፣ባቢሎናውያንን ሁሉ እንደ ኰብላይ አመጣለሁ።

15. እኔ እግዚአብሔር፣ የእናንተ ቅዱስ፣የእስራኤል ፈጣሪ፣ ንጉሣችሁ ነኝ።”

16. በባሕር ውስጥ መንገድ፣በማዕበል ውስጥ መተላለፊያ ያበጀ፣ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤

17. እንደ ገና ላይነሡ እዚያው እንዲተኙ፣እንደ ጧፍ ኵስታሪ ረግፈው እንዲጠፉ፣ሠረገሎችንና ፈረሶችን፣ሰራዊቱንና ደጀኑን በአንድነት ያወጣ እንዲህ ይላል፤

18. “የቀደመውን ነገር አታስቡ፤ያለፈውን እርሱ።

19. እነሆ፤ አዲስ ነገር አደርጋለሁ፤እርሱም አሁን ይበቅላል፤ አታስተውሉትምን?በምድረ በዳም መንገድ አዘጋጃለሁ፤በበረሓም ምንጭ አፈልቃለሁ፤

20. የምድረ በዳ አራዊት፣ቀበሮና ጒጒት ያከብሩኛል፤በምድረ በዳ ውሃ፣በበረሓም ምንጭ እሰጣለሁና።ለመረጥሁት ሕዝቤ ውሃ እሰጣለሁ፤

21. ለራሴ ያበጀሁት ሕዝብምስጋናዬን ያውጅ ዘንድ ይህን አደርጋለሁ።

ኢሳይያስ 43