አስቴር 9:14-25 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

14. ንጉሡም ይህ እንዲሆን አዘዘ። በሱሳ ዐዋጅ ተነገረ፤ ዐሥሩንም የሐማ ወንዶች ልጆች ሰቀሏቸው።

15. በሱሳ የሚኖሩ አይሁድ አዳር በተባለው ወር በዐሥራ አራተኛው ቀን በአንድነት መጡ፤ በሱሳም ሦስት መቶ ሰዎች ገደሉ፤ በምርኮው ላይ ግን እጃቸውን አልዘረጉም።

16. በዚህ ጊዜ በሌሎች በንጉሡ አውራጃዎች የሚኖሩ የተቀሩት አይሁድ ራሳቸውን ለመከላከልና ከጠላቶቻቸውም ለመገላገል ተሰበሰቡ፤ ከሚጠሏቸውም ሰባ አምስት ሺህ ገደሉ፤ በምርኮው ላይ ግን እጃቸውን አልዘረጉም።

17. ይህ የሆነው አዳር በተባለው ወር ዐሥራ ሦስተኛ ቀን ነበር፤ በዐሥራ አራተኛው ቀን ዐረፉ፤ ዕለቱንም የተድላና የደስታ ቀን አድርገው ዋሉ።

18. በሱሳ የሚኖሩ አይሁድ ግን በዐሥራ ሦስተኛውና በዐሥራ አራተኛው ቀን ተሰብስበው ነበር፤ ከዚያም በዐሥራ አምስተኛው ቀን ዐረፉ፤ ዕለቱንም የተድላና የደስታ ቀን አድርገው ዋሉ።

19. በየመንደሩ የሚኖሩ የገጠር አይሁድ፣ የአዳርን ወር ዐሥራ አራተኛ ቀን የተድላና የደስታ፣ እርስ በርሳቸውም ስጦታ የሚለዋወጡበት ቀን አድርገው የሚያከብሩት ከዚሁ የተነሣ ነው።

20. መርዶክዮስ የተፈጸሙትን እነዚህን ድርጊቶች ጻፈ፤ ደብዳቤ አዘጋጅቶም በመላው የንጉሥ ጠረክሲስ አውራጃ በቅርብና በሩቅ ለሚገኙት አይሁድ ሁሉ ላከ፤

21. የላከውም የአዳርን ወር ዐሥራ አራተኛና ዐሥራ አምስተኛ ቀን በየዐመቱ እንዲያከብሩ ነው፤

22. የሚያከብሩበትም ምክንያት አይሁድ ከጠላቶቻቸው ዕረፍት ያገኙበት፣ ሐዘናቸው ወደ ደስታ፣ ልቅሷቸውም ወደ ክብረ በዓል የተለወጠበት ቀን ስለ ሆነ ነው። ቀኖቹንም የተድላና የደስታ ቀኖች አድርገው፣ እርስ በርሳቸውም የምግብ ስጦታ እየተለዋወጡና ለድኾችም ስጦታ እየሰጡ እንዲያከብሩ ጻፈላቸው።

23. ስለዚህ አይሁድ መርዶክዮስ የጻፈላቸውን ለመፈጸምና የጀመሩትን በዓል ለማክበር ተስማሙ፤

24. ምክንያቱም የአይሁድ ሁሉ ጠላት የሆነው የአጋጋዊው የሐመዳቱ ልጅ ሐማ አይሁድን ለማጥፋት አሢሮ ነበር፤ ሊፈጃቸውና ሊያጠፋቸውም ፉር የተባለ ዕጣ ጥሎ ነበር።

25. ሤራው በንጉሡ ዘንድ እንደ ታወቀ ሐማ በአይሁድ ላይ የሸረበው ሤራ በገዛ ራሱ ላይ እንዲጠመጠም፣ እርሱና ወንዶች ልጆቹም በዕንጨት ላይ እንዲሰቀሉ የጽሑፍ ትእዛዝ አስተላለፈ።

አስቴር 9