ምሳሌ 5:3-14 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

3. የአመንዝራ ሴት ከንፈር ማር ያንጠባጥባልና፤አንደበቷም ከቅቤ ይለሰልሳል፤

4. በመጨረሻ ግን እንደ እሬት ትመራለች፤ሁለት አፍ እንዳለውም ስል ሰይፍ ትሆናለች።

5. እግሮቿ ወደ ሞት ይወርዳሉ፤ርምጃዎቿም በቀጥታ ወደ ሲኦል ያመራሉ።

6. ስለ ሕይወት መንገድ ደንታ የላትም፤መንገዶቿ ዘወርዋራ ናቸው፤ ለእርሷ ግን አይታወቃትም።

7. እንግዲህ፣ ልጆቼ ሆይ፤ አድምጡኝ፤ከምነግራችሁ ቃል ፈቀቅ አትበሉ።

8. መንገድህን ከእርሷ አርቅ፤በደጃፏም አትለፍ፤

9. ይኸውም ጒብዝናህን ለሌሎች፣ዕድሜህንም ለጨካኞች እንዳትሰጥ ነው፤

10. ባዕዳን በሀብትህ እንዳይፈነጥዙ፣ልፋትህም የሌላውን ሰው ቤት እንዳያበለጽግ ነው።

11. በዕድሜህ መጨረሻ ታቃሥታለህ፤ሥጋህና ሰውነትህ ሲከዳህ።

12. እንዲህም ትላለህ፤ “ምነው! ተግሣጽን ጠላሁ፤ልቤስ ምነው! መታረምን ናቀ፤

13. የመምህሮቼን ቃል አልሰማሁም፤አሰልጣኞቼንም አላደመጥኋቸውም፤

14. በመላው ጉባኤ ፊት፣ወደ ፍጹም ጥፋት ተቃርቤአለሁ።”

ምሳሌ 5