መሳፍንት 8:8-27 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

8. ከዚያም ወደ ጵኒኤል ሰዎች ሄዶ ያንኑ ጥያቄ አቀረበላቸው፤ የእነርሱም መልስ የሱኮት ሰዎች ከሰጡት መልስ ጋር አንድ ዐይነት ነበር።

9. እርሱም የጵኒኤልን ሰዎች፣ “በድል አድራጊነት በሰላም ስመለስ ከተማችሁን የምትጠብቁበትን ይህን ግንብ አፈርሰዋለሁ” አላቸው።

10. በዚህ ጊዜ ዛብሄልና ስልማና ዐሥራ አምስት ሺህ ከሆነ ሰራዊታቸው ጋር ቀርቀር በተባለ ስፍራ ነበሩ፤ ይህም ከምሥራቅ ሕዝቦች ከተውጣጣውና በጦር ሜዳ ከወደቀው መቶ ሃያ ሺህ ሰይፍ ታጣቂ ሰራዊት የተረፈው ነበር።

11. ከዚያም ጌዴዎን ተነሣ፤ ከኖባህና ከዮግብሃ በስተ ምሥራቅ የሚኖሩ ዘላኖች የሚሄዱበትን መንገድ ተከትሎ በጠላት ሰራዊት ላይ በድንገት አደጋ ጣለ።

12. ሁለቱ የምድያም ነገሥታት ዛብሄልና ስልማና ሸሹ፤ ጌዴዎን ግን አሳዶ ያዛቸው፤ መላ ሰራዊታቸውንም እጅግ በታተነው።

13. ከዚህ በኋላ የኢዮአስ ልጅ ጌዴዎን በሐሬስ መተላለፊያ በኩል አድርጎ ከጦርነቱ ተመለሰ፤

14. እርሱም የሱኮት ሰው የሆነ አንድ ወጣት ማረከ፤ መረመረውም፤ ወጣቱም የሰባ ሰባት የሱኮት ሹማምትና የከተማዪቱንም አለቆች ስም ጻፈለት።

15. ከዚያም ጌዴዎን ወደ ሱኮት ሰዎች መጥቶ እንዲህ አላቸው፤ “ ‘ለደከሙት ሰዎችህ እንጀራ እንሰጥ ዘንድ ዛብሄልና ስልማና በእጅህ ገብተዋልን’ በማለት ያላገጣችሁብኝ ዛብሄልና ስልማና እነዚሁላችሁ።”

16. ጌዴዎን የከተማዪቱን አለቆች ወሰደ፤ በምድረ በዳ እሾኽና አሜኬላ በመቅጣት የሱኮትን ሰዎች ትምህርት ሰጣቸው።

17. እንዲሁም በጵኒኤል ያለውን የከተማ መጠበቂያ ግንብ አፈረሰ፤ የከተማዪቱንም ሰዎች ገደለ።

18. ዛብሄልና ስልማናንም፣ “በታቦር ላይ የገደላችኋቸው ሰዎች እንዴት ያሉ ነበሩ?” በማለት ጠየቃቸው።እነርሱም፣ “ሁሉም እንዲህ እንዳንተ ያሉ የንጉሥ ልጆች የሚመስሉ ናቸው” አሉት።

19. ጌዴዎንም፣ “እነርሱ የእናቴ ልጆች ወንድሞቼ ናቸው፤ ባትገድሏቸው ኖሮ እኔም እንደማልገድላችሁ በሕያው እግዚአብሔር ስም አረጋግጥላችሁ ነበር።” ብሎ መለሰላቸው።

20. ከዚያም ወደ በኵር ልጁ ወደ ዮቴር ዘወር ብሎ፣ “ግደላቸው” አለው፤ ዮቴር ግን ትንሽ ልጅ ነበርና ስለ ፈራ ሰይፉን አልመዘዘም።

21. ዛብሄልና ስልማናም፣ “የሰው ጒልበቱ እንደ ሰውነቱ መጠን ነውና አንተው ራስህ ግደለን አሉት፤ ጌዴዎንም ተነሥቶ ገደላቸው፤ በግመሎቻቸው አንገት ላይ የነበሩትንም ጌጦች ወሰደ።

22. እስራኤላውያንም ጌዴዎንን፣ “ከምድያማውያን እጅ ታድገኸናልና አንተ፣ ልጅህና የልጅ ልጅህ ግዙን” አሉት።

23. ጌዴዎን ግን መልሶ፣ “እኔም ሆንሁ ልጄ አንገዛችሁም፤ የሚገዛችሁ እግዚአብሔር ነው” አላቸው።

24. እርሱም፣ “አንድ የምጠይቃችሁ ነገር አለኝ፤ ይኸውም እያንዳንዳችሁ ከምርኮ ካገኛችሁት ውስጥ የጆሮ ጒትቻችሁን እንድ ትሰጡኝ ነው” አላቸው፤ የወርቅ ጒትቻ ማድረግ የእስማኤላውያን ባህል ነበርና።

25. እነርሱም መልሰው፤ “ደስ እያለን እንሰጥሃለን” አሉት፤ ወዲያው ልብስ አነጠፉ፤ በላዩም ላይ እያንዳንዳቸው ከማረኩት ውስጥ የጆሮ ጒትቻ ጣል ጣል አደረጉለት።

26. ሌሎቹን ጌጣጌጦች ይኸውም የዐንገት ሐብሉን ከነእንጥልጥሉ፣ የምድያም ነገሥታት ይለብሱት የነበረውን ሐምራዊ ልብስ ወይም በግመሎቻቸው ዐንገት ላይ ያሉትን ጌጦች ሳይጨምር ጌዴዎን በጠየቃቸው መሠረት የሰጡት የወርቅ ጒትቻ ክብደት ሺህ ሰባት መቶ ሰቅል ያህል መዘነ።

27. ጌዴዎን በወርቁ ኤፉድ ሠራ፤ በተወለደበትም ከተማ በዖፍራ አኖረው። እስራኤልም በሙሉ ኤፉዱን በማምለክ ስላመነዘሩ፣ ኤፉዱ ለጌዴዎንና ለቤተ ሰቡ ወጥመድ ሆነ።

መሳፍንት 8