2 ዜና መዋዕል 18:16-28 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

16. ከዚያም ሚካያ “እስራኤል ሁሉ እረኛ እንደሌላቸው በጎች በተራሮች ላይ ተበታትነው አየሁ፤ እግዚአብሔርም፣ ‘እነዚህ ሰዎች ጌታ የላቸውም፤ እያንዳንዱም በሰላም ወደየቤቱ ይመለስ’ ብሎአል” ሲል መለሰ።

17. የእስራኤልም ንጉሥ ኢዮሣፍጥን፣ “ስለ እኔ ክፉ ብቻ እንጂ፣ ደግ ትንቢት እንደማ ይናገር አልነገርሁህምን?” አለው።

18. ሚካያም በመቀጠል እንዲህ አለ፤ “እንግዲህ የእግዚአብሔርን ቃል ስማ፤ እግዚአብሔር በዙፋኑ ላይ ተቀምጦ፣ የሰማይም ሰራዊት ሁሉ በቀኙና በግራው ቆመው አየሁ።

19. እግዚአብሔርም፣ ‘የእስራኤል ንጉሥ አክዓብ በሬማት ገለዓድ ላይ ዘምቶ እዚያው እንዲሞት ማን ያሳስተው?’ አለ።“አንዱ አንድ ሐሳብ፣ ሌላውም ሌላ ሐሳብ አቀረበ።

20. በመጨረሻም አንድ መንፈስ ወደ ፊት ወጥቶ፣ በእግዚአብሔር ፊት በመቆም፣ ‘እኔ አሳስተዋለሁ’ አለ።“እግዚአብሔርም፣ ‘እንዴት አድርገህ?’ ሲል ጠየቀው።

21. “እርሱም፣ ‘እሄድና በነቢያቱ ሁሉ አፍ የሐሰት መንፈስ እሆናለሁ’ አለ።“እግዚአብሔርም፣ ‘እንግዲያውስ ሂደህ አሳስተው፤ ይሳካልሃልም’ አለው።

22. “አሁንም እነሆ፣ እግዚአብሔር በእነዚህ ነቢያትህ አፍ የሐሰት መንፈስ አኖረ፤ እግዚአብሔርም ጥፋት አዞብሃል”።

23. ከዚያም የክንዓናም ልጅ ሴዴቅያስ ወጥቶ ሚካያን በጥፊ መታውና፣ “ለመሆኑ የእግዚአብሔር መንፈስ አንተን ያነጋገረህ፣ በየት በኩል አልፎኝ ነው?” አለው።

24. ሚካያም፣ “ለመሸሸግ ወደ እልፍኝህ በምትሄድበት በዚያ ዕለት ታገኘዋለህ” አለው።

25. ከዚያም የእስራኤል ንጉሥ እንዲህ ሲል አዘዘ፤ “ሚካያን ይዛችሁ ወደ ከተማዪቱ ገዥ ወደ አሞንና ወደ ንጉሡ ልጅ ወደ ኢዮአስ መልሳችሁ ላኩት፤

26. እነርሱንም፣ ‘ንጉሡ፣ ይህን ሰው እስር ቤት አስገቡት፤ በደህና እስክመለስም ድረስ ከደረቅ ቂጣና ከውሃ በስተቀር ምንም አትስጡት ብሎአል’ በሏቸው።”

27. ሚካያም፣ “አንተ በደኅና ከተመለስክማ እግዚአብሔር በእኔ አልተናገረም ማለት ነው!” አለ፤ ቀጥሎም፣ “እናንተ ሰዎች ሁላችሁ ስሙኝ” አለ።

28. ስለዚህ የእስራኤል ንጉሥና የይሁዳ ንጉሥ ኢዮሣፍጥ ወደ ሬማት ገለዓድ ወጡ።

2 ዜና መዋዕል 18